በሥጋዉ ሆነ በመንፈሳዊ ወንበር ላይ ያሉ ሆኑ ግለሰቦች እንዲያውቁት!

✍ ተክለ ኪዳን 

"ለእኔም ፡- ዘመኑ ቀርቧልና የዚህን መጽሐፍ ትንቢት ቃል በማኅተም አትዝጋዉ፡፡ ዓመፀኛዉ ወደ ፊት ያምፅ፣ ርኩሱም ወደ ፊት ይርከስ፣ ጻድቁም ወደ ፊት ጽድቅ ያድርግ፣ ቅዱሱም ወደ ፊት ይቀደስ አለ፡፡
እነሆ በቶሎ እመጣለሁ፣ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራዉ መጠን እከፍል ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር ነዉ አለ፡፡ አልፋና ዖሜጋ ፈተኛዉና ኋለኛዉ መጀመሪያዉና መጨረሻዉ እኔ ነኝ" ዮሐ. ራእይ 22፡ 10-13 በማለት ነበር የሁሉ ፈጣሪና አስገኝ አምላክ አልፋና ዖሜጋ የሆነዉ ቸሩ መድኃኔዓለም እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ፤ በሥጋ ቅድስት ድንግል ማርያም በተዋሕዶ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰዉ ሆኖ የዛሬ ሁለት ሺህ ዓመት ገደማ በምድር ላይ ተገልጾ ትዉልዱ ምን ማድረግ እንዳለበትና እደሌለበት አስተምሮ፣ ታላቅ ተስፋቸውን አሳውቆ፣ የጨለማ አሰራርን አጋልጦ፣ መገሰጽ ያለባቸውን ገስጾ፣ ተአምራትንና ፈዉስ አድርጎ፣ የተለያየ መከራን በመቀበል ተስቅሎ፣ በሥጋዉ ሞቶ፣ የሰው ልጆች በሥጋ ምት ህልውናቸው እንደማይጠፋና ሕያዋን መሆናቸውን እንዲያስተውሉ በተጨባጭ ትንሣኤንና እርገትን አሳይቶ ወደ ቀደመ ክብሩ ከተመለሰ በኋላ ለወንጌላዊዉ ቅዱስ ዮሐንስ ቃል በቃል የተናገረዉ ሕያዉ ቃል ነዉ፡፡

ከቃሉ እንደምንረዳዉ ከእግዚአብሔር የሆነዉን መቀበል አለመቀበል እንዲሁም እንደ ቃሉ መኖርና አለመኖር የእያንዳንዱ ግለሰብ ነጻ ምርጫና ወሳኔ ነዉ፡፡ ነገር ግን ግሰለቡ ዋጋ ሊቀበል ሆነ ዋጋ ሊከፍል የሚችለዉ እንደ መታዘዙና አለመታዘዙ፣ የተባለውን ተግባራዊ እንደማድረጉና እንደ አለማድረጉ ነው እንጂ፤ እንደ ፍላጎቱና ምኞቱ አይደለም፡፡ ይህ ፍርድ የሚጸናዉ ደግሞ በምድርም በሰማይም ነዉ፡፡ ይኸዉም ምንም እንኳን ምድራዊ ዘመናችን ከዚህች ምድር ስንለይ ከምንኖረዉ ሕያዉነት ዘመን አንጻር የዐይን ቅጽበት ዘመን ቢሆንም፤ ዓመፀኛ ሰዉ በምድርም ነፍሱ በተገለጸችበት ሥጋ አማካይነት በተለያየ መልኩ ይቀጣል፡፡ ነፍሱ ከሥጋ እንደተለየች ደግሞ እንደ ርኩሳን መናፍስት ጸጋ በጎደለዉና ጎስቋላ በሆነ አካል ተገልጾ፤ በመጀመሪያ በሲኦል፣ ከፍርድ ቀን በኋላ በገሃነመ እሳት ለሕያዉነት ዘመን እንደ ዓመፃዉ፣ ክህደቱ፣ ርኩሰቱ፣ ግፍ ተግባሩ ደረጃ ዋጋ ይከፍላል፣ ይቀጣል፡፡ የእግዚአብሔር ፍቅርና ቸርነት የትየለሌ እንደሆነ ሁሉ ፍርዱና ቅጣቱም እጅግ ጥብቅ ነዉ፡፡ 

እንኳን በግልጽ በተግባር በምንፈጽመዉ ኃጢአት ይቅርና በንግግራችን፣ ከሕሊናችን ፈልቆ በምንጽፈዉ፣ በስድባችን፣ ወደ ዉጭ በማይገለጸዉ በሕሊናችን በምንፈጽመዉ የዓመፃና የኃጢአት ንግግርና ሐሳብ፤ እዉነተኛ ንስሐ ካልገባንበትና በሕሊናችንም ካልተጸጸትንበት በስተቀር እንደምንጠየቅበትና ዋጋ እንደምንከፍለበት ነዉ የእግዚአብሔር ቃል የሚያሳዉቀን፡፡ ለዚህም ነዉ በማቴ.ምዕ.12፣ቁ. 36 "እኔ እላችኋለሁ ሰዎች ስለሚናገሩት ስለ ከንቱ ነገር ሁሉ በፍርድ ቀን መልስ ይሰጡበታል፤ ከቃልህ የተነሣ ትጸድቃለህና ከቃልህ የተነሣ ትኮነናለህ፡፡"፣ እንዲሁም በማቴ. ምዕ.5፣ ቁ.22 "ወንድሙን ደንቆሮ የሚል የገሃነመ እሳት ፍርድ ይገባዋል፡፡"፣ በማቴ. ምዕ.5፣ 28 "ወደ ሴት ያየ ሁሉ ለዝሙት የተመኛትም ያን ጊዜ በልቡ ከእርሷ ጋር አመንዝሯል" በማለት የተናገረዉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በድፍረትና በትዕቢት መንፈስ ቅዱስን የሚሳደቡ የንስሐ ልብ ስለማያገኙ ከነኃጢአታቸዉ ለፍርድ እንደሚቀርቡ የሚገልጽልን፤ ማቴ. ምዕ.12 ቁ.32 "በሰዉ ልጅ ላይ ቃል የሚናገር ሁሉ ይሰረይለታል፤ በመንፈስ ቅዱስ ላይ ግን የሚናገር ሁሉ በዚህ ዓለም ቢሆን ወይም በሚመጣዉ አይሰረይለትም፡፡" ይላል፤
በተቃራኒ ደግሞ የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ እንደ ቃሉ የሚኖርና የሚፈጽም፤ በምድራዊ ሕይወቱ ዘመን የተለያየ ጸጋን ያገኛል፤ ይባረከል፡፡ ነፍስ ከሥጋዉ እንደተለየች ደግሞ እንደ ቅዱሳን መላእክት ክብርና ጸጋ ባለዉ አካል በመገለጽ በቀጥታ ወደ ገነት ገብቶ ገነታዊ አኗኗር ይኖራል፡፡ ከፍርድ ቀን በኋላ ደግሞ በመንግሥተ ሰማያት በቅዱሳን መላእክት አኗኗር ለሕያዉነት ዘመን ይኖራል፡፡

ሌላዉ ከእግዚአብሔር የሆነዉን ማንም ፍጡር ሊያስቀረዉ ሆነ ሊያጠፋዉ እንዲሁም ሊያዘገየው አይችልም፡፡ ከእግዚአብሔር ያልሆነዉ ደግሞ ከእግዚአብሔር መስሎ ለጊዜዉ ቢቀርብና ቢታይ እንኳ፤ በጊዜዉ ይጋለጣል፣ ይጠፋል፣ አይጸናም።
በመሆኑም በመንፈሳዊ ወንበር ላይ ከላይ እስከታች ያላችሁ አባቶችና ወንድሞች!

ከተጠያቂነት ለመዳን ሆነ ሰማያዊ ዋጋ ለማግኘት ከእግዚአብሔር እዉነት ጋር ብቻ ከመሰለፍና ከእግዚአብሔር የሆነዉን እዉነት ይዞ ተጋድሎ ከማድረግ ዉጭ፤ እንደ ጸሐፍት ፈሪሳዉያን እና አይሁድ ካህናት አለቆች፤ መሪያችሁን መንፈስ ቅዱስ ሳይሆን እዉቀታችሁን፣ ዝናችሁን፣ ክብራችሁን፣ ሥልጣናችሁን፣ ምድራዊ ጥቅማችሁን ካደረጋችሁ፤ እግዚአብሔርን በእዉነትና በመንፈስ ልታመልኩት ሆነ አማኙንም በእዉነት ልታገለግሉ፣ መልካም ፍሬ ልታፈሩ አትችሉም፡፡ ይልቁኑ ከእግዚአብሔር እዉነት በተቃራኒ ቆማችሁ ከእግዚአብሔር የሆኑትን ልታሳድዱ፣ ልትቃወሙ፣ ልትተቹ፣ ልትወነጅሉ፣ ልታሳስሩ፣ ልትገሉ ትችላላችሁ፡፡ በዚህም ምክንያት እንደ ጸሐፍት ፈሪሳዉያን እና አይሁድ ካህናት አለቆች በምድርም በሰማይም በእጥፍ ዋጋ ልትከፍሉ ትችላላችሁ፡፡ ስለዚህ እንደ ምሁሩ ፈሪሳዊዉ ጻድቁ ኒቆዲሞስ፤ በቅንና እዉነተኛ አእምሮ ሆናችሁ በእግዚአብሔር ስም የመጣዉን ማንኛዉንም ነገር በእዉነትና በመንፈስ ቅዱስ መርምራችሁ እዉነተኛ ምስክርነት ብቻ እንድትሰጡና ከእዉነት ጋር እንድትሰለፉ ወንድማዊ ጥሬዬ ነዉ፡፡

ሌላዉ መሪያችሁ የሥጋና የደም ስሜት እንዲሁም የጨለማዉ ገዥ የዲያብሎስ መንፈስ ያደረጋችሁ በሥጋዊ ወንበር ላይ የተቀመጣችሁ ከላይ እስከ ታች ያላችሁ ፓለቲከኞች!

ለእናንት ያለኝ ወንድማዊ ምክርና ጥሪ፤ በእናንተዉ ዘመን የተከሰቱትን ያለፉትን ታሪኮች በማስተዋል ተገንዘቡ፡፡ እያንዳንዱ ክንዋኔና ለዉጥ በእግዚአብሔር እዉቅና የተከናወነና እግዚአብሔር በወሰነዉ ጊዜ የሆነ እንጂ፤ ግለሰቦች ሆኑ ቡድኖች እንዲሁም ድርጅቶችና መንግሥታት፤ ለለውጡ ምክንያትና መሳሪያ ከመሆን ዉጭ በራሳቸዉ ሥልጣንና ኃይል ያመጡት አይደለም፡፡ እኔ ከማዉቀዉ ከቅርብ ዘመን ብንጀምር፤ የደርግ ኢሠፓ መንግሥት ምን ያህል በጦር የተጠናከረና የስለላ መዋቅሩ የከበደ እንዲሁም የመናገር፣ የመጻፍ ነጻነት ምን ያህል ቢገድብ፤ የዓመፃ፣ የክህደት፣ የግፍ ጽዋዉ ሲሞላ ግን፤ በጥቂቶቹ የሕወሐትና የሻዕቢያ ጦር ሊሸነፍና መታሰቢያው ሊጠፋ ችሏል፡፡ በሥርዓቱ ዉስጥ የነበሩት ከላይ እስከ ታች ያሉ ባለሥልጣናትና ካድሬዎች ማንም ሊታደጋቸዉና ሊያድናቸው ሳይችል ለእስር፣ ለሞት፣ ለስደት፣ ለመከራ ተዳርገዋል፡፡ እግዚአብሔር በወሰናት ቀን የ17 ዓመት የአዛዥና ናዛዥ፣ የፈላጭና ቆራጭ የባለጊዜ ዘመናቸዉ ተደምድሞ ለባለተረኞቹ ለሕወሐት ኢሕአዴግና ለሻዕቢያ ቡድኖች ወንበራቸውን አስረክበዉ ሄደዋል፡፡
የሕወሐት ወያኔ ኢሕአዴግ መንግሥት ምን ያህል ኢትዮጵያዉያን አንድ እንዳይሆኑ በዘርና በቋንቋ ሕዝቡን ቢከፋፍል፣ በዐማራዉ ማኅበረስብና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች ላይ ጥላቻንና በቀልን ቢዘራ፣ ጥቃት ቢያስፈጽም፣ በየመንደሩ የስለላ መዋቅሩን ቢያጠናክርና አባላቱን ቢያበዛ ፣ እንዲሁም በጦር ኃይሉና በስለላዉ ቢመካ፤ የዓመፃዉ፣ የክህደቱ፣ የርኩሰቱና የግፉ ጽዋ ሲሞላ፤ የተማመኑባቸዉና የተመኩባቸዉ ሁሉ ሳይታደጓቸዉና ሳያድኗቸው ራሳቸዉ በፈጠሯቸዉ ድርጅቶች አባላትና በ27 ዓመት ዉስጥ ባፈሩት ትዉልድ አማካይነት እንዳልነበሩ የሆኑትና ከባለጊዜነታቸዉ፣ ከአዛዥ ናዛዥነታቸዉ፣ ከፈላጭ ቆራጭነታቸዉ የተወገዱትና ለእስር፣ ለሞት፣ ለስደት፣ ለመከራ የተዳረጉት፡፡ እግዚአብሔር በወሰናት ቀን የ27 ዓመት የአዛዥና የናዛዥ፣ የፈላጭና ቆራጭ የባለጊዜነት ዘመናቸዉ ተደምድሞ ለተረኛዉ ኦህዴድ ኦነግ ብልጽግና መንግሥት ወንበራቸዉ ተላልፎ የተሰጠዉ፡፡
አሁን ባለ ጊዜ የሆነዉ ኦህዴድ ኦነግ ብልጽግና መንግሥት ደግሞ ከፈጠረዉ ከሕወሐት ኢሕአዴግ መንግሥት ዉድቀትና ጥፋት ትምህርት ወስዶ ለቅን ሐሳብ፣ ለመልካም ተግባር፣ ለእዉነተኛ አገልግሎት መሰለፍ ሲገባዉ፣ በዓመፃ ላይ ዓመፃ፣ በክህደት ላይ ክህደት፣ በርኩሰት ላይ ርኩሰት፣ በግፍ ላይ ግፍ በመጨመር የባለ ጊዜነት ዘመኑን እጅግ እጅግ እያሳጠረና ራሱን ለዉድቀትና ለጥፋት እያዘጋጀ መሆኑን በእምነት ዉስጥ ላለ ሰዉ በሚገባ ይታወቀዋል፡፡ እግዚአብሔር የወሰናት ቀን ስትደርስ "የእኔ ናቸዉ፣ ይታደጉኛል፣ የሥልጣን ዘመኔን ያስረዝሙልኛል…ወዘተ" ብሎ የሚመካባቸዉና የሚተማመንባቸዉ ማንኛዉም ነገር፤ እግዚአብሔር ከፈቀደላቸዉ ዘመን በላይ የአንድ ቀን እድሜ እንኳ የማይቀጥሉለትና የማይታደጉት መሆኑን በቅርቡ የምንመለከተዉ ይሆናል፡፡

ስለዚህ በፓለቲካ ቁማር፣ በበቀልና በተንኮል፣ በክፋትና በግፍ፣ በማስፈራራትና በጭከና፣ እንዲሁም ከንቱ በሆነ ሥጋዊ መጠበብ የባለ ጊዜነት ዘመናችሁን ማስረዘም አይቻላችሁምና ፤ አጠፋፋችሁ የከፋ እንዳይሆን ስላለፈዉ የዓመፃ፣ የክህደት፣ የርኩሰት፣ የግፍ ተግባራችሁ በእዉነትኛ ንስሐ ተመልሳችሁ እጃችሁን ለእግዚአብሔር እንድትሰጡና ሕዝቡንም ይቅርታ በመጠየቅ ወንበሩን በአራቱም ማእዘን የእግዚአብሔርን ፈቃድ ብቻ ለሚፈጽሙና ለሚያስፈጽሙ ለእግዚአብሔር ባለሟሎችና ለእመ አምላክ ለድንግል ማርያም ምርጥ ልጆች አሳልፋችሁ ብትሰጡ በሥጋም በነፍስም ተጠቃሚ ትሆናላችሁ፡፡ "በያዝነዉ አቋምና ተግባር ነዉ የምንቀጥለዉ፣ በፓለቲካ ቁማር አንቻልም፣ ዓላማችንና ግባችንን እናሳካለን…ወዘተ" በማለት የምትጸኑ ከሆነ፤ የእግዚአብሔር ቁጣና ፍርድ እንዲሁም ድንቅ ሥራ ምን እንደሚመስል ሁላችንም በቅርቡ የምንመለከተዉ ይሆናል፡፡

በስተመጨረሻ ለማንኛዉም የአዳም ዘር የማስተላልፈዉ፤ ምንም እንኳን እግዚአብሔር በተለያዩ ባለሟሎቹና እዉነተኛ መልእክተኞቹ በኩል ከእርሱ የሆነዉን መልእክት በተለያየ ጊዜ ያስተላለፈና አሁንም እያስተላለፈ ቢሆንም፤ እግዚአብሔር በእዉቀታቸዉና በጽድቃቸዉ ራሳቸዉን የሚያመጻድቁትንና የሚያስታብዩትን "ዐዋዊና ሊቅ ነን፣ ታዋቂና ዝነኛ ነን፣ ከእኛ በላይ የሚያገለግልና ለእዉነት የሚመሰክር የለም፣ …ወዘተ" የሚሉትን ለማሳፈር ሲል፤ ኃጢአተኛነቴን፣ በደለኛነቴን፣ ደካማነቴን፣ ስንፍናዬን ከማመን ዉጭ አንዳች መልካም ነገር አለኝ ብዬ የማላምነዉን ተራና መሃይም ዲዳ ሰዉ በመጠቀም ከመስከረም 2003 ዓ.ም ጀመሮ እስከ ነሐሴ 2010 ዓ.ም ድረሰ አራት መልእክታትን አጽፎኝ ለትዉልዱ እንዳቀርብ አድርጓልና፤ እነዚህ "በእግዚአብሔር ስም የመጡ መልእክቶች፣ እዉነታዎች፣ ምሥጢራት፣ ትንቢታት፣ እዉቀቶች..ወዘተ ምንድናቸዉ?" ብሎ ለማወቅና ከእግዚአብሔር እዉነት ጋር ለመሰለፍ ፍላጎቱ ያለዉ እንዲሁም ለሌላው ወገኑ ለማድረስ የሚፈልግ ሰዉ ካለ፡

1. መስከረም 2003 ዓ.ም የተጻፈዉን "የኢትዮጵያና የዓለም የመጨረሻ ፍርድ አፈጻጸም ዉሳኔ" በሚል ርእስ የተጻፈዉን https://bit.ly/40V5uyE ሊንክ በመክፈት በቀጥታ አዉርዶ ማንበብ ሆነ ለሌው ወገን ማድረስ ይችላል፡፡

2. ከመስከረም 2004 ዓ.ም አጋማሽ እስከ ታኅሣሥ 2004 ዓ.ም አጋማሽ ድረስ "የጨለማዉ ገዥ ተግባርና ንግግር" በሚል ርእስ የተጻፈዉን https://bit.ly/3nuIWXA ሊንክ በመክፈት በቀጥታ አዉርድ ማንበብ ይችላል፡፡

3. ከነሐሴ 18/2004 ዓ.ም እስከ ታኅሣሥ 12/ 2005 ዓ.ም "ታላቅ የብርሃን ተስፋ ለኢትዮጵያንና ለዓለም" በሚል ርእስ የተጻፈዉን https://bit.ly/3NsOUmD  ሊንክ በመክፈት በቀጥታ አዉርዶ ማንበብ ይችላል፡፡

4.  በነሐሴ 2010 ዓ.ም በፍልሰታ ጾም በሁለተኛዉ ሱባኤ "የሚመጣዉ መከራና ፍርድ" በሚል ርእስ የተጻፈዉን https://bit.ly/3Af2Xo1 ሊንክ በመክፈት በቀጥታ አዉርዶ ማንበብ ሆነ ለሌላው ወገን ማድረስ ይችላል፡፡

ይላል፤ ምናልባት ባለማወቅና ባለማስተዋል ከእግዚአብሔር እዉነት ጋር እየተላተሙና እየተጋጩ ያሉ ትንሽ ቅንነትና እዉነተኛነት ያላቸዉ ሰዎች ካሉ፤ ባለቀ ሰዓት እንኳ በእዉነተኛ ንስሐ ተመልሰዉ ከእግዚአብሔር እዉነት ጋር እንዲሰለፉና አንድነት እንዲፈጥሩ ጥሪ የሚያቀርበዉ፤ አሁንም ወደፊትም ከእግዚአብሔር መልእክት ጋር በተገናኘ በሚያስተላልፈዉ አገልግሎት ከማንም ግለሰብ ሆነ ቡድን እንዲሁም ድርጅት ሆነ መንግሥት አንዳች የተለየ ጥቅም የማይፈልገዉና፤ ፍላጎቱ፣ ምኞቱ፣ ጸሎቱ ሰዎች ሁሉ እግዚአብሔር ያደረገላቸዉን ከሕሊና በላይ የሆነውን ታላቅ ዉለታ፣ ፍቅርና ዋጋ ከፈላ አስተዉለዉ እንደፈቃዱ እንዲመላለሱና እንዲኖሩ በኋላም ለገነት ለመንግሥተ ሰማያት እንዲበቁ ብቻ የሆነ፤ በኢትዮጵያዊና ኢትዮጵያዊነት የሚያሚምነዉ፣ እግዚአብሔራዊ የሆነዉ የኮኮብ ምልክት የሌለበት ልሙጡ አረንጋዴ ብጫ ቀይ ሰንደቅ ዓላማ በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም በመላዉ ዓለም ክፍ ክፍ እንዲል የሚፈልገዉ፤

ኢትዮጵያ የሥላሴ የክብራቸዉ መገለጫና መመስገኛ ምድር እንዲሁም ርስተ ድንግል ማርያም መሆኗን የሚያምነዉ፣ ኢትዮጵያና ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነቷ የመከራዉንና የፈተናዉን ዘመን አልፈዉ አሁን ባለነዉ ትዉልድ በቅርቡ ከእግዚአብሔር ከመደምደሚያ ቁጣና ጠረጋ በኋላ በሚመጣዉ በእዉነተኛዉ የኢትዮጵያ ትንሣኤ ዘመን ለተራፊዉ ትዉልድ የዓለም ብርሃንና የዓለሙ ገዥ እንደሚሆኑ በእምነትና በተስፋ ከሚጠብቁት ዉስጥ አንዱ የሆነዉ፤ በገጠርም በከተማም በበበረሃም ያለችዉ የአንዲቷ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ልጅ የሆነዉና ነፍስ ከሥጋዉ እስከምትለይ ድረስ እንደ ቅድስት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እግዚአብሔራዊ እምነትና ሥርዓት እንዲሁም አስተምህሮና ትዉፊት የሚጸነዉ፤ የእግዚአብሔርን እውነት ከመግለጥና ከመመስከር ወጭ የግሉ ስውር ዓላማና ግብ የሌለው፤ ለሌለውም የጥፋት ዓላማና ግብ መሳሪያ የማይሆነው፤ በኢትዮጵያና በተዋሕዶ እምነት ፈጽሞ የማይደራደረዉ ተክለኪዳን፡፡ 

ተጻፈ በመከራና በፈተና ዉስጥ ካለችዉ፤ ዓመፃ፣ ክህደት፣ ርኩሰት፣ ግፍ ከነገሠባት ሀገረ እግዚአብሔር ከተባለችዉ ከባለተስፋይቱ ቅዲስቲቱ ኢትዮጵያ 

፳፯፥፰፥፳፻፲፭
Share on Google Plus

ስለ የተለጠፈበት ቀን

    Blogger Comment
    Facebook Comment