ኢትዮጵያ የምትድነዉ በፋኖ መንገድ ብቻ መሆኑን አትርሱት!


✍ ሸንቁጥ አየለ

ከስብሃት ነጋ: ከጀዋር መሃመድ: ከህዝቅኤል ጋቢሳ: ከገዱ አንዳርጋቸዉ ስብስብ ኢትዮጵያን የሚያድን ነገር ጠብ ይላል ብለህ ካሰብክ ያዉ ወያኔ ኢትዮጵያን ከተቆጣጠረችበት አሁን ኦህዴድ/ኦነግ ሀገር እየመራ እስካለበት ያለዉን ሁኔታ ለራስህም ለትዉልድም ለማዉረስ ተዘጋጅ::

በተለይም ፍጹም ኢትዮጵያዊ ነኝ: የኢትዮጵያ ህዝብ አንድ ነዉ ብለህ የምታስብ ወይም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ የሆንክ: ወይም ነገደ አማራ የሆንክ ሁሉ ተስፋህን ቁረጥ:: ከስብሃት ነጋ: ከጀዋር መሃመድ: ከህዝቅኤል ጋቢሳ: ከገዱ አንዳርጋቸዉ ስብስብ ኢትዮጵያን የሚያጠፋ እንጂ ኢትዮጵያን የሚያድን አንዳች ነገር አይፈጠርም::

ለምን ብለህ ጠይቅ እማ?

ኢሎን መስክ አንድ የሚገርም አባባል አለዉ:: "ሰዉ  ሀሳቡን አይለዉጥም::ከሀሳቡ ጋር ይሞታል እንጂ:: ስለዚህ ምክንያትም ሰዉ መሞት አለበት::ምክንያቱም አዳዲስ ሀሳብ ላላቸዉ አዳዲስ ትዉልዶች ቦታዉን ለመልቀቅ" ይላል:: ይሄ አባባሉ ትክክለኛ እና በብዙ ጥናቶች የተረጋገጠ ነዉ::እና  ሰሞኑን መስክ ከትረምፕ ቢጣላ ጊዜ  ብድግ ብሎ "ግራ ወይም ቀኝ ጽንፍ ላይ ያልቆመ ማዕከላዊ አስተሳሰብ ያለዉ ፓርቲ (centerist )  እመሰርታለሁ"  የሚል ነገር ሲያራምድ ባይ ከት ብዬ ሳቅሁኝ::

መስክ ትርፍ የሚያመጣ ከመሰለዉ  ማንኛዉንም የመንግስት ሰራተኛ ወይም የግል ሰራተኛ ጠርጎ የሚያባርር: በብዙ ሚሊዮን ችግረኞችን በመላዉ አለም ይደግፍ የነበረ ዩ ኤስ ኤይድን ጠርቅሞ የዘጋ: የአሜሪካ ተቋማዊ ቀጣይነትን ያለጥናት ያተረማመሰ ጽንፈኛ ሰዉዬ ነዉ:: ይሄ ሰዉ ድንገት ብድግ ብሎ ግራ ቀኙን አስተዉሎ ብዙሃኖች የሚጠቀሙበትን ቀመር የሚያንሰላስል የፖለቲካ ፓርቲ እመሰርታለሁ ቢልህ ሀሰት ማለት አለብህ::

ቢመሰርትም እራሱን ማዕከል አድርጎ ትርፉን የሚቆጥርበትን እንጂ የሰዉ ልጆችን የጋራ ጥቅም የሚያገኙበትን የፖለቲካ ፕሮግራም ይዞ ሊመጣ አይችልም::ባለፈዉ ቢልጌት እና የቢልጌት ባለቤት "እረ  ዩ ኤስ ኤይድን ከመዝጋትህ በፊት የሚደገፈዉን ህዝብ ዞር ዞር ብለህ ተመልከት " የሚል መልዕክት ቢሰዱለት "እስኪ ዩ ኤስ ኤይድ ስለተዘጋ አንድ የሞተ ህጻን ወይም ሴት አሳዩኝ " ብሎ ቁጭ አለ::መስክ ከዚህ ሀሳቡ ሳይላቀቅ ነዉ እንግዲህ ወደዚያኛዉ አለም የሚሄደዉ::በራሱ አባባል ግራ ቀኙን የሚመለከት ፓርቲ ሳይሆን ለመስክ የሚሰራዉ ጽንፈኛ ፓርቲ ነዉ::

ለኢትዮጵያ ጥፋት ስለሆኑት ፖለቲከኞች ጉዳይ እንቀጥል

የጀዋር ሰላም :የህዝቄል ሰላም : የስብሃት ነጋ ሰላም የነሱ ነገድ የበላይነት የሚኖርበት ሁኔታን የሚያካትት መድረክ ካለ ብቻ ነዉ::የገዱ ሰላም ደግሞ ሆዱ ሳይጎድል ትንሽ ስልጣን ብጤ የሚያገኝበት ሁኔታ ከተፈጠረ ሚሊዮኖች በእነስብሃት:ጀዋር እና ህዝቄል ቢጨፈጨፉ ግድም አይሰጠዉም:: ይሄ የነዚህ ሰዎች የአሰተሳሰብ ስሪት ነዉ::

የልደቱስ የአስተሳሰብ ስሪት ምንድን ነዉ? አንድ ምሳሌ ላንሳ::ልደቱ ከመዓህድ ተጣላሁ ብሎ የመዓህድን ወጣቶች ሰብስቦ በዬነጴጥሮስ የሚባል ተቃዋሚ መሰል የወያኔ ሰላይ ቢሮ ዉስጥ ጠባብ ማረፊያ  ቢጤ አግኝቶ ገባ::እናም በዬነ ጴጥሮስ ጠዋት ማታ ከአፉ የማይለዬዉን "ነፍጠኛ" የሚለዉን ሀረግ እያነሳ ልደቱን ይኮረኩመዋል::ልደቱ በመናገር ብቻ ሰዎችን ማሳመን እችላለሁ ብሎ ያምናልና በንግግር በዬነን ለማሳመን ብዙ ጣረ::አልቻለም::ሲመረዉ ተጣልቶ ከበዬነ ቢሮ ጥሎ ጠፋ::ሆኖም በዬነ በጋዜጣ "ለምን ተጣላችሁ" ሲባል "በትምክህተኝነታቸዉ" ሲል መለሰ::

በዬነ ከእነ ሀሳቡ ወደ አፈሩ ገባ:: ኢትዮጵያን የሚጠሉ ሰዎች ከእነ ሀሳባቸዉ ወደ ምድር ይገባሉ:: ጎሰኞችም እንዲሁ::ሰዎች በተለይም በፓርቲ ከተደራጁ ብኋላ ከሀሳባቸዉ ጋር ወደ ምድር እስኪገቡ ሀሳባቸዉ ላይ ሙጭጭ ብለዉ ይሞታሉ:;ደጋጎችም ክፉዎችም ከሀሳባቸዉ ጋር ወደ ምድራቸዉ አፈር እስኪመለሱ የሁላችን እጣ ፋንታ ይሄዉ ነዉ::

ልደቱም የማያሳምናቸዉን ሰዎች ለማሳመን ሲደክም እና ሲናገር ኖሮ እንዲሁ ይሆናል እንጂ ለኢትዮጵያ ከሚበጁት ጋር ተስማምቶ አይሰራም:: ልደቱ እዉነት ኢትዮጵያን ማዳን ቢፈልግ ኖሮ የፋኖ መነሳት እጅግ ትልቅ እድል ፈጥሮለት ነበር:: በመልካም አንደበቱ ፋኖዎችን ወደ ኢትዮጵያዊነት እንዲመጡ እያበረታታ (እየተሰደበም ቢሆን) በተጨባጭ ደግሞ እጎናቸዉ ቆሞ እንዲጠናከሩና አንድ እንዲሆን ብዙ ስራ መስራት ይችል ነበር::ግን ልደቱ ጉልበቱን የት ማጥፋት እንዳለበት አያዉቅም::ስለተናገረ ብቻ ማሳመን የሚችል ይመስለዋል::በዬነ ፔጥሮስን ማሳመን ያልቻለ ሰዉ ስብሃት ነጋን እና ህዝስቅዬስን ሊያስምን?

ህዝቅያስ እንደሆነ የሰዉ ልጅ ፍጥረቱ አንድ አይደለም ብሎ የሚያምን የራሱን ጎሳ ከሰዉ ዘር አንድነት የነጠለ ሰዉ ነዉ::እንዲህ አይነቱን ሰዉ እዉነት በሀሳብ አንድነት ማሳመን ይቻላል:? በአለም ላይ ያሉ ሀይማኖቶች እስላም:ክርስቲያን አይሁድ እና ሌሎችም በጋራ አንድ የሚስማሙበት ነገር ቢኖር ሰዉ ሁሉ የተፈጠረዉ በእግዚአብሄር ነዉና ሰዉ አንድ ዘር ነዉ ብለዉ ያምናሉ:: ሆኖም ህዝቃየስን ጠይቀዉማ :: "አማራን ትግሬን :ጉራጌን እንቶኔነ እንቶኔን  የፈጠራቸዉ ሌላ አምላክ ሲሆን እኔን የፈጠረኝ ግን .. " ብሎ የሰዉን ፍጥረት አንድነት አፈር ያበላልሃል:: እረ እንዴዉም በጣም የሚገርም እና የሚያሳፍር ነገር ያስተምርሃል::

ከህዝቅያስ ጋር ምን አይነት የፖለቲካ የሀሳብ አንድነት መፍጠር እንደሚቻል አይታወቃም::በርግጥ መጀመሪያ በሮ "አዲስ አበባ:ሸዋ;ሶማሌ : ከፊል የአማራ ክልል እንዲሁም በራያ በኩል ትግራይ ለእኔ ነገድ ይገባል:: አቢይ አህመድ ይሄን ሁሉ ለእኔ ነገድ እንዲሆን ያልሰራዉ እናቱ አማራ ስለሆነች ነዉ" ይልሃል::በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ አማራዎች ሲፈናቀሉ እና ሲጨፈጨፉ ህዝቄል አልሰማም::አከተመ እነ ህዝቅያስ ከፍም ቢሉ ዝቅም ቢሊ ከዚህ የዘለለ የፖለቲካ ፍልስፍና የላቸዉም::ከእነዚህ ጋር ምን ትነጋገራለህ? እንደገዱ የባርነት ሀሳብ ዉስጥ የወደቅህ ሰዉ ከሆንክ ብቻ ቁጭ ብለህ የነዚህን ሀሳብ ለማድመጥ አይቀፍህም::

እና አሁን እነ ስብሃት የሚሰሩት ምንድን ለማትረፍ ነዉ?

ድራማ ነዉ የሚሰሩት::ሁሉም የሚያደርገዉ ድራማ ነዉ:: ሁሉም ሀሳቡን የሚያሟላበት ክፍተት ለመፍጠር ድራማ ያከናዉናል:: ከላይ እንደተባባባልነዉ ሀሳባቸዉን ለዉተዉ ኢትዮጵያን የሚያድን ነገር ላይ ግን ፈጽሞ አይደርሱም::ሁሉም በጋራ የባርነት ሀሳብ ዉስጥ :ከሰዉነት በታች የሆነ የሀሳብ ቀለበት ዉስጥ የወደቁ ምናምንቴ ጸረ ኢትዮጵያዊ ናቸዉ::

የፋኖ ተግህዳሮት?

በዉጭ ሀገር የሚኖሩ አክቲቪስት ነን የሚሉ ከዉጭ መንግስታት ጋርም የቀረቡ በዋናነትም የአማራ ጥቅም አራማጅ መስለዉ ለአማራ ህዝብ መታረጃ ቢላዎ ከሚስሉ ሃይሎች ጋር የሚሞዳሞዱ የፋኖ ትልቅ ተግዳሮት ናቸዉ::አማራ ነን ይላሉ::የአማራ ወዝ ቀርቶ እሴቱ የላቸዉም::

ፋኖዉን በዚህና በዚያ የሚያዋክቡ : እነ ኦኤም ኤን ሚዲያ ላይም የሚጣዱ : ህዉሃት ሲጠራቸዉም አቤት የሚሉ:ከእነገዱ ጋርም የሚሞዳሞዱ : ከብአዴን በጎን ገንዘብ እየተቀበሉ ለአቢይ የሚሰሩ: በረከት በሞላበት የም ዕራብ ሀገራት እየኖሩ እራሳቸዉን ለዉጠዉ የራሳቸዉን ኑሮ እንኳን ለመኖር ያልፈቀዱ: የሲቪል ማህበራት የመሰረቱ ሆኖም እርስ በርስ የሚጠላለፉትን ሁሉ መቁጠር ስጀምር ይደክመኛል::አማራ ብለዉ ተደራጅተዉ መስማማት አቅቷቸዉ ሳለ ከኦነጋዊ/ህዉሃታዊ አስተሳሰብ ጋር ተስማምተዉ ኢትዮጵያን የሚያድን ነገር ይዘዉ ሲመጡ አስበህዋል?

ኢትዮጵያዊስ

በቀጣይ መከራ የሚገጥምህ ኢትዮጵያዊነትን የምትወድ:የኢትዮጵያ ህዝብ አንድ ህዝብ ነዉ:መላዋ ኢትዮጵያ ነጻ መዉጣት እና የሰዉ ልጆች የእኩለነት እና የአንድነት ሀገር መሆን አለባት:የህግ የበላይነት ብቻ ህዝብን ይዳኘዋል:የጎሳ ፖለቲካ በህግ መታገድ አለበት ብለህ የምታምነዉ ወገንስ ምን እያረግህ ነዉ? ፈርተህ ወይም ተደናግረህ ቁጭ ብለሃል::ቢያንስ እንኳን አትነጫነጭም እና  እራስህን መልሰህ ለጎሰኞች አዘጋጅተሃል ማለት ነዉ::የሚሻልህ ፋኖን መደገፍ እና ፋኖ የኢትዮጵያ የነጻነት ሰራዊት እንዲሆን ማበረታታት ነዉ::ምርጫዉ ይሄዉ ብቻ ነዉ::ፋኖ የአማራ ሰራዊት ብቻ ነዉ እያሉ የሚወላገዱ የብአዴን ቅፍቅፎችን አትስማ::ፋኖ የኢትዮጵያ የነጻነት ሰራዊ ነዉ የሚሆነዉ::ስለዚህ ፋኖዉ እንዲያሸንፍ ማገዝ ይገባል::

የተዋህዶ እምነት ተከታዮች ነገርስ?

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ክርስትና እምነት ተከታዮች መድሃኒዓለም እራሱ በእንቢልታ ካልቀሰቀሳችሁ በቀር ኢትዮጵያን ላለማዳን ለሽ እና ለጥ ብላችሁ በኩታችሁ ተጀባቡናችኋል:: የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን ተዋህዶን አቢይ አህመድ ሊዉጣት አፉን ከፍቶ እናንተ ፖለቲካ አያገብናኝም ብላችሁ ትሽሞነሞናላችሁ::

ማጠቃለያ

ለማንኛዉም ኢትዮጵያ የምትድነዉ በፋኖ መንገድ ብቻ መሆኑን አትርሱት

Share on Google Plus

ስለ የተለጠፈበት ቀን

    Blogger Comment
    Facebook Comment