❖❖❖[ትንቢተ ሶፎንያስ ምዕራፍ ፪]❖❖❖
- ፩፤፪ እናንተ እፍረት የሌላችሁ ሕዝብ ሆይ፥ ትእዛዝ ሳይወጣ፥ ቀኑም እንደ ገለባ ሳያልፍ፥ የእግዚአብሔርም ቍጣ ትኵሳት ሳይመጣባችሁ፥ የእግዚአብሔርም ቍጣ ቀን ሳይደርስባችሁ ተሰብሰቡ፥ ተከማቹም።
- ፫ እናንተ ፍርዱን የጠበቃችሁ የምድር ትሑታን ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ፈልጉ፤ ጽድቅንም ፈልጉ፥ ትሕትናንም ፈልጉ፤ ምናልባት በእግዚአብሔር ቍጣ ቀን ትሰወሩ ይሆናል።
- ፬ ጋዛ ትበረበራለች፥ አስቀሎናም ባድማ ትሆናለች፤ አዞጦንንም በቀትር ወደ ውጭ ያሳድዱአታል፥ አቃሮንም ትነቀላለች።
- ፭ በባሕር ዳር ለሚኖሩ ለከሊታውያን ሕዝብ ወዮላቸው! የፍልስጥኤማውያን ምድር ከነዓን ሆይ፥ የእግዚአብሔር ቃል በአንተ ላይ ነው፥ የሚቀመጥብህም ሰው እንዳይኖር አጠፋሃለሁ።
- ፮ ቀርጤስም የእረኞች መኖሪያና የመንጎች በረት ይሆናል።
- ፯ የባሕሩም ዳር ለይሁዳ ቤት ቅሬታ ይሆናል፥ በዚያም ይሰማራሉ፤ አምላካቸው እግዚአብሔር ይጐበኛቸዋልና፥ ምርኮአቸውንም ይመልሳልና በአስቀሎና ቤቶች ውስጥ ማታ ይተኛሉ።
- ፰ በሕዝቤም ላይ ያላገጡባትን፥ በድንበራቸውም ላይ እየታበዩ የተናገሩባትን የሞዓብን ማላገጥና የአሞንን ልጆች ስድብ ሰምቻለሁ።
- ፱ ስለዚህ የእስራኤል አምላክ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። እኔ ሕያው ነኝና በእርግጥ ሞዓብ እንደ ሰዶም፥ የአሞንም ልጆች እንደ ገሞራ፥ የሳማ ስፍራና የጨው ጕድጓድ ለዘላለምም ምድረ በዳ ሆነው ይኖራሉ፤ የሕዝቤም ቅሬታ ይበዘብዛቸዋል፥ ከወገኔም የተረፉት ይወርሱአቸዋል።
- ፲ በሠራዊት ጌታ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ አላግጠዋልና፥ እየታበዩም ተናግረዋልና ይህ ስለ ትዕቢታቸው ያገኛቸዋል።
- ፲፩ እግዚአብሔር በእነርሱ ላይ የተፈራ ይሆናል፥ የምድርንም አማልክት ሁሉ ያከሳቸዋል፤ በአሕዛብም ደሴቶች ሁሉ ላይ የሚኖሩ ሰዎች ሁሉ በስፍራቸው ሆነው ለእርሱ ይሰግዳሉ።
- ፲፪ እናንተም ኢትዮጵያውያን ደግሞ፥ በሰይፌ ትገደላላችሁ።
- ፲፫ እርሱም በሰሜን ላይ እጁን ይዘረጋል፥ አሦርንም ያጠፋል፤ ነነዌንም ባድማ፥ እንደ በረሃም ደረቅ ያደርጋታል።
- ፲፬ መንጎችም የምድርም አራዊት ሁሉ በውስጥዋ ይመሰጋሉ፤ ይብራና ጃርት በዓምዶችዋ መካከል ያድራሉ፤ ድምፃቸው በመስኮቶችዋ ይጮኻል፤ የዝግባም እንጨት ሥራ ይገለጣልና በመድረኮችዋ ላይ ጥፋት ይሆናል።
- ፲፭ ተዘልላ የተቀመጠች፥ በልብዋም። እኔ ነኝ፥ ከእኔም በቀር ሌላ የለም ያለች ደስተኛይቱ ከተማ ይህች ናት፤ አራዊት የሚመሰጉባት ባድማ እንዴት ሆነች! በእርስዋ በኩል የሚያልፈው ሁሉ እጁን እያወዛወዘ ያፍዋጫል።
♱ ትንቢተ ሶፎንያስ ♱
የትንቢተ ሶፎንያስ ዋና ዓላማ ንስሐ ብቸኛውና አማራጭ የሌለው የመዳን መንገድ መኾኑን መግለጽ፣ አለቆቹንና በየትኛው ደረጃ ያለውን ሰው መገሰጽ፣ እንዲኹም በይሁዳ ላይ ሊመጣ ያለውን ቊጣ (በከለዳውያን እጅ ወደ ምርኮ መኼድ) ማሳወቅ ነው፡፡
ምንም እንኳን መጽሐፉ የሚዠምረው ሊመጣ ያለውን ፍርድ በማሳወቅ ቢኾንም የሚጨርሰው ግን በምስጋና ነው፡፡ ይኸውም በአብዛኞቹ የነቢያት መጻሕፍት የምናስተውለው አካኼድ ነው፡፡ አብዛኞቹ ነቢያት አስቀድመው የእግዚአብሔር ፍርድ ምን እንደኾነ ይገልጣሉ፤ በመጨረሻም ለኹሉም ተስፋ ድኅነትን ይሰጣሉ፡፡ በተለይ ደግሞ ይኸው ድኅነት ሊመጣ ካለው መሲሕ ጋር በማያያዝ ነው የሚነግርዋቸው፡፡ ትንቢተ ሶፎንያስም አካኼዱ እንዲኽ ነው፡፡ አስቀድሞ የሰው ወዳጁ እግዚአብሔር ሐዘን እንደምን እንደኾነ ይናገራል፡፡ እግዚአብሔር የሰው ልጆችን እንዲኽ እያፈቀራቸው እነርሱ ግን በኃጢአት በበደል በመውደቃቸው እጅግ እንዳዘነ ይገልጣል፡፡ በመጨረሻ ግን እንደተናገርነው በሐሴት በደስታ ይጨርሳል፡፡
ትንቢተ ሶፎንያስ አስቀድሞ በይሁዳ መንግሥት ላይ ሊመጣ ያለውን የእግዚአብሔርን ፍርድ ያሳውቃል፡፡ በመቀጠል በትውልድ ኹሉ ላይ የሚታየውን የእግዚአብሔር ትዕግሥት እንደምን ጥልቅ እንደኾነ ይናገራል፡፡ ቀጥሎም ለእግዚአብሔርና ለሕዝቡ በሚያሳዩት ልክ ያልኾነ አያያዛቸው አሕዛብም ጭምር እንደሚፈረድባቸው ይናገራል፡፡ በመጨረሻ ግን መጽሐፉ ስለ አዲሲቷ ኢየሩሳሌም፥ ሕዝብም አሕዛብም አንድ አድርጋ ስለምትሰበስበው ቤተ ክርስቲያን ያበሥራል፡፡
ነቢዩ ሶፎንያስ የንጉሥ ቤተ ሰብ እንደመኾኑ በቤተ መንግሥቱ አከባቢ የነበረውን ብልግናም ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ምንም ሳይፈራና ሳያፍር መናገሩም ስለዚኹ (ንጉሣዊ ቤተ ሰብ በመኾኑ) ነው፡፡
በአጠቃላይ መጽሐፉን እንደሚከተለው መክፈል እንችላለን፡-
፩. አብዛኞቹ አይሁዳውያን ልክ እንደ ሰሜናዊው ክፍል “እግዚአብሔር ለምርኮ አሳልፎ ይሰጠናል” ብለው አስበዉም አልመዉም አያውቁም፡፡ ይኽን ያሉበት ምክንያት ደግሞ ይሁዳ የዋናው ቤተ መቅደስ መናኸርያ በመኾኗ፣ ከተማይቱ በተለያየ ጊዜ የእግዚአብሔር ከተማ መኾኗ ስለተገለጸ እግዚአብሔር ሊያፈርሳት አይችልም ሕዝቡንም ለጠላት አሳልፎ አይሰጥም የሚል አጉል የኾነ እምነት ስለነበራቸው ነው፡፡ ከዚኽም የተነሣ አምልኮተ ጣዖትን ከአምልኮተ እግዚአብሔር ጋር ቀላቅለው ያስኼዱ ነበር፡፡ ምንም እንኳን አብዛኛው ሕዝብ ከንጉሥ ኢዮስያስ ጋር ቢተባበርም፥ መመለሱ አፍኣዊ እንጂ ውሳጣዊ (ከልብ) አልነበረም ያልነውም ስለዚኹ ነው፡፡ ነቢዩ ሶፎንያስ ግን፥ በዚኹ በአንደኛው ምዕራፍ፡- “ታላቁ የእግዚአብሔር ቀን ቀርቧል” በማለት ይሁዳ ወደ ምርኮ እንደምትኼድ ቤተ መቅደሱም እንደሚፈርስ አስረግጦ ይነግራቸው ነበር /ምዕ. ፩/፤
፪. በምዕራፍ አንድ ላይ እግዚአብሔር እስራኤልንና ይሁዳን ከመቅጣት እንደማይመለስ ተናግሯል፤ ምክንያቱም ክፋትን ስለሚጠላ፡፡ ነገር ግን ምንም እንኳን ሕዝቡን ለመገሰጽ አሦርንና ባቢሎንን ቢጠቀምም አሦርና ባቢሎን መታበይ ከዠመሩ፣ ሕዝቡን ባልተፈለገ መንገድ የሚያንገላቱ ከኾነ ግን እንደሚፈርድባቸው በኹለተኛው ምዕራፍ ይናገራል /ምዕ. ፪/፤
፫. በክፋቷ ስለቀጠለች፣ ለእግዚአብሔር ድምጽ ጆሮዋ ስለተደፈነ፣ የእግዚአብሔርን ቁንጥጫ አልቀበል ስላለች፣ ራሷን ወደ አምላኳ ለማቅረብ ስላልወደደች፥ እግዚአብሔር ኢየሩሳሌምን “ዓመፀኛይቱ ከተማ፣ የረከሰች ከተማ፣ አስጨናቅይቱ ከተማ” ብሎ ይጠራታል፡፡ እንዲኽ በመኾኗም ከሌሎች አገራት ጋር የእግዚአብሔር ቊጣ በእርሷ ላይ እንደሚመጣ፣ በእርሷ ፈንታም ሌላ አዲስ ኢየሩሳሌም እንደምትመሠረት፣ በአዲሲቱ ኢየሩሳሌም ሕዝብም አሕዛብም እንደሚሰበሰቡና በንጹሕ ልቡናቸውም እግዚአብሔርን እንደሚያመልኩ፤ እግዚአብሔርም በመካከላቸው እንደሚያድር በምዕራፍ ሦስት ላይ ይናገራል፡፡ እርሷም ቤተ ክርስቲያን ናት /ምዕ. ፫/፡፡
♱ እኛስ ከዚኽ ምን እንማራለን? ♱
እግዚአብሔር ቀናተኛ አምላክ ነው፡፡ ካህናተ እግዚአብሔር ከካህናተ በኣል ጋር ኅብረት እንዲኖራቸው ፈጽሞ አይሻም፡፡ እንኳንስ እግዚአብሔር ይቅርና ሰውም የገዛ ንብረቱ ከሌላ ሰው ንብረት ጋር እንዲቀላቀል አይሻም፡፡ አንድ ባል ሚስቱ ከሌላ ወንድ ጋር አላስፈላጊ ነገር እንድታደርግ አይሻም፡፡ ካደረገች ግን ይፈታታል፡፡ እግዚአብሔርማ እንዴት?
እግዚአብሔር ስነ ፍጥረትን የፈጠረው በእነርሱ አልፈን ወደ ፈጣሪያቸው እንድንዘልቅ እንጂ በእነርሱ ላይ እንድናቆም አይደለም፡፡ ጣዖት የሚፈጠረው ግን እንዲኽ ያደረግን እንደኾነ ነው፡፡ እናም በስነ ፍጥረታቱ ላይ ስናቆም እግዚአብሔርን እንዳንመለከት ከልክለውናልና እነዚኽን ማሰናከያዎች ከፊታችን ያስወግዳቸዋል፡፡ እንኳንስ ስነ ፍጥረታት ይቅርና የገዛ አካላችንም ጣዖት ከኾነብንና እግዚአብሔርን ከማየት ከጋረደን ያጠፋቸዋል /ኢሳ.፫፡፲፮- ፍጻሜ/፡፡
እግዚአብሔር ምድር ብቻ እንድንኾን አይፈልግም፤ እንደተፈጠርንበት ዓላማ ሰማያውያንም ጭምር እንጂ፡፡ ሰማያውያን ስንኾን እግዚአብሔር ከእኛ ቤት (ከሰውነታችን) ያድራል፡፡ ብቻውን ሳይኾን ከቅዱሳን መላእክቱ ጋር ያድራል፡፡ ምድራውያን ብቻ የኾንን እንደኾነ ግን ቤታችን የሸረሪት ድር ማድሪያ ይኾናል (የዲያብሎስና የሠራዊቱ ማፈንጫ ይኾናል)፡፡
ንስሐ ሊመጣ ካለው የእግዚአብሔር ቊጣ ይሰውራል፡፡ ንስሐ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር ዝቅ ብሎ በባሮቹ ቤት (በእኛ) እንዲያድር ያደርጓል፡፡ ንስሐ ጸጋ እግዚአብሔር በእኛ ላይ እንዲትረፈረፍ ያደርጋል፡፡ የንስሐ ትልቁ ዕንቅፋት ግን ተዘልሎ መቀመጥ ነው፡፡ የንስሐ ትልቁ ማለቆ እግዚአብሔር ለሕይወታችን እንደሚያስፈልገን ሳይሰማን ሲቀር ነው፡፡
እግዚአብሔር ሲቀጣ ሰው እንደሚቀጣ አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር ቅጣት የፍቅር ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቁንጥጫ የአባትነት ነው፡፡ የእግዚአብሔር ተግሳጽ አሮጌይቱን ኢየሩሳሌም ከማንነታችን ነቅሎ አዲሲቱን ኢየሩሳሌም ለመገንባት ነው፡፡ የእግዚአብሔር ተግሳጽ አንካሳው ልባችንን ለማቅናት ነው፤ ጠላትን ለመጣል ነው፤ ክፉውን እንዳናይ ነው፤ ስድብን ለማራቅ ነው፤ ከምርኮ ለመመለስ ነው፤ ለከበረ ስምና ለምስጋና ነው፡፡
♱ ተመስጦ ♱
ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ተብለኽ በቅዱሳን መላእክትና ሰዎች የምትመሰገን ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር ሆይ! እጅግ ደንዳኖች ብንኾንም ስላልተውከን እናመሰግንኻለን፡፡ ወደ ዕቅፍኽ እንድንመለስ በማሳጣትም ጭምር ስለምትጠራን እናመሰግንኻለን፡፡ ጸጋኽን ለመስጠት በምስጢራዊቷ የተግሳፅ እጅኽ ስለምትጠራን እናመሰግንኻለን፡፡ ንስሐ ገብተን ከአንተው አከባታችን ጋር እንድንታረቅ በሚያስደንቅ አጠራር ሹክ ስለምትለን እናመሰግንኻለን፡፡ ማንንም ስለማትንቅ እናመሰግንኻለን፡፡ በርኽ ኃጥአንን ለመቀበል ዘወትር ክፍት ነውና እናመሰግንኻለን፡፡
ቸርና ሰው ወዳጅ ሆይ! ወዳንተ የማንመለሰው ስላልወደድን አይደለም፤ ብርታቱ ስለሌለን እንጂ፡፡ እንኪያስ አትተወን፡፡ ሰማያዊው ሙሽራችን ሆይ! አሮጌይቱን ኢየሩሳሌም ከማንነታችን አስወግድልና አዲሲቱን ኢየሩሳሌም ሥራልን፡፡ አማኑኤል ሆይ! ከእኛ ጋር ኹንና ኹለንተናችንን ሰርግ ቤት አድርግልን፡፡ ሰርግ ቤት ኾነንም ከቅዱሳን ኹሉ ጋር እንድናመሰግንኽ ፍቀድልን፡፡ አሜን!!!
Blogger Comment
Facebook Comment