የኢትዮጵያ ተዋህዶ ቤተ ክርስትያን በ "ኔቸር" መፅሔት!

ዘርአዳዊት ዘ-ኢትዮጵያ


[ኢትዮጵያ አውታር ጥር 22 ቀን 2011 ዓ.ም.] -  ዝነኛው የሳይንስ መጽሔት " Nature" አንድ ግሩም የሆነ ጽሑፍ  "የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ደኖች እየቀነሰ ለመጣው የብዝሃ ሕይወት የመጨረሻ መጠለያ ናቸው" በሚል ርዕስ ሥር በትናንትናው ዕለት ይዞልን ቀርቧል።

የደን ሥነ–ምሕዳር ተመራማሪው ወንድማችን አለማየሁ ዋሴ፡በ ከአውሮፓውያን እና አሜሪካውያን ባለሙያዎች ጋር በመተባበር በኢትዮጵያ ዓብያተክርስቲያናት ደኖች ውስጥ በሚገኙት የዛፎች፣ የአበቦች፣ የአእዋፍ እና የነፍሳት ዝርያዎች ላይ የተለያዩ የምርምር ሥራዎችን በማካሄድ ላይ ነው።


በቆላማ አካባቢዎች ከሚገኙት ይልቅ ቀዝቃዛ እና እርጥበት ያላቸው የቤተክርስቲያን ደኖች ሙሉ አመት ቅጠል የተሸከሙ ዛፎችን፣ ቁጥቋጦዎችን እና አበባዎችን ያቀፉ ናቸው። እነዚህ አዕጽዋታት ከመርዛማ ካርቦን አየሩን ይከላከላሉ፣ የውሃን ንጽሕና ይጠብቃሉ፣ የአፈር መሸርሸርን ይቀንሳሉ እንዲሁም የተፈጥሮ መድሃኒትን ያቀርባሉ።


በእኔ በኩልም፤ አብዛኛዎቹ የቤተክርስቲያን ቪዲዮዎቼ ላይ የሚታዩት ብርቅ ዛፎችና አበቦች፣ እንዲሁም የምንሰማቸው ደስ የሚሉ ወፎችና ነፍሳት ይህን ይመሰክራሉ።


አቶ አለማየሁ ዋሴና ባልደረቦቹ ከተናገሯቸው ግርሙ የሆኑ ዓረፍት ነገሮች መካከል፦
+ አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት አሁን ማሕበረሰባቸውን ለማበረታት ደኖቻቸውን ለማስፋፋት እየሞከሩ ነው፤ይህም አበረታች የሆነ ተግባር ነው።


+ በኢትዮጵያ ጫካማ የሆነ ቦታ ካየን፥ መሀከል ላይ በርግጥ ቤተክርስቲያን እንዳለ የማወቅ እድል ይኖረናል።
+ ደኖቹ የመጠለያ፣ ፀሎት የማድረጊያ እና የመቃብር ቦታዎች ሆነው ያገለግላሉ።

+ አብዛኛው የአገሪቱ ጫካ እያደገ የመጣውን የአገሪቱን የሕዝብ ቁጥር ለመመገብ ሲባል ለግብርና መስዋእትነት ወስዷል። የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥር ከ 100 ሚሊዮን በላይ ነው፣ ይህም በዓለም 12 ኛ ደረጃ ትልቁ ነው። በተለይ ከ 1974-1991 ዓ.ም በሀገሪቱ የኮሚኒዝም ሥርዓት፡ በ "መሬት ለአራሹ" ዘመን፡ የደን ጭፍጨፋው አሳዛኝ የሆነ ደረጃ ላይ ደርሶ ነበር፤ በተለይም የቤተ ክርስቲያኒቱን ሰፋፊ ቦታዎች በመውረስ ደኖቻቸውን እየመነጠሩ ለእርሻ እንዲውሉ አድርገዋቸዋል። በአሁን ዘመን በአገሪቱ 5% ብቻ በደን የተሸፈነ ሲሆን፤ በሀያኛው ክፍለ ዘመን እስከ 45 በመቶ ነበር።
+ ምን ያህል ስብጥር እንደጠፋ በውል አናውቅም ፥ ነገር ግን ከጠበቅነው በላይ በጣም ጉልህ የሆነ የስብጥር መጠን መትረፉን እናውቃለን።


+ የደን ብዝሃ–ህይወት ስብጥርን መጠበቅ ለእርሻ
በጣም አስፈላጊ ነው፤ ምክንያቱም በዓብያተ ክርስቲያናቱ ጫካዎች ውስጥ የሚኖሩት ብዙዎቹ ወፎች እና ነፍሳት ሰብሎችን ለማዳቀል እና ተባይን ለመቆጣጠር ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረክታሉና ነው።
በጀርመን የ ሙኒክ ዩኒቨርሲቲ የራሄል ካርሰን የአካባቢና
ማሕበረሰብ ማዕከል ዲሬክተር የሆኑት ክሪስቶፍ ማከስ
አክለው እንዲ ብለዋል፦


+ ከግማሽ በላይ ለሚሆኑት የኢትዮጵያ ሕዝቦች እናት የሆነችው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ደኖቿ የሰማይ መንግስትን በምድር ላይ የሚወክሉ ናቸው፤እያንዳንዱ ፍጥረት የእግዚአብሔር ስጦታ ስለሆነ መኖሪያ ይፈልጋል።
+ የተፈጥሮ አካባቢዎች መንፈሳዊ ክልል አካል የሆኑት እነዚህ ደኖች በባህልና በሳይንሳዊ መልኩም በጣም አስፈላጊ ናቸው።"
Share on Google Plus

ስለ የተለጠፈበት ቀን

    Blogger Comment
    Facebook Comment